Monday 4 January 2016


የአጼ ምኒልክ ዘመናዊ ጥበብን መውደድና ወደ ሀገራቸው ለማስገባት የሚያረጉትን ጥረት በእንግሊዝ ሀገር ሆኖ ይሰማ የነበረው /Bentley/ ቤንትሌይ ምኒልክ ታሪኩን ሰምተው ለማየት እጅግ የጓጉለትን መኪና ለምን አልወስድላቸውም ብሎ ተነሳ: ሃሳቡንም "ዌል ሲልይ ቱል ኤንድ ሞተር ማኒፋክቸሪን" /well sell toll and motors manufacturers/ ለተባለ ድርጅት አቅርቦ ከድርጅቱ ጠንካራ መኪናን አገኘ ከዚህም በኋላ /Bentley/ ቤንትሌይ ከጓደኛው ዌልስ ጋር በመሆን መኪናዋን ይዘው ጉዞ ወደ ኢትዮዽያ ጀመሩ ከ27 ቀን የባህር ጉዞ በኋላ ጅቡቲ ደረሱ ከጅቡቲም ድሬደዋ ገቡ: በድሬደዋና በሐረርም ጥቂት ቀናትን ቆይተው ከዚያ ጉዞዋቸውን ወደ አዲስ አበባ አደረጉ: አሸዋማ ቦታዎች ላይ ሰዎች ድንጋይ እያነጠፉ መንገዷን እያቀኑ: አንዳንዴም በበቅሎ እየተጐተተች: ድንጋያማ ቦታና ወንዝ ሲያጋጥም ደግሞ በሰው ሸክም እየተሻገረች: ተራራ ሲሆን እየተገፋች ታኀሳስ 20 ቀን 1900 ዓ/ም የመጀመሪያዋ መኪና አዲስ አበባ ደረሰች: ታኅሳስ 22 ቀን 1900ዓ/ም አጼ ምኒልክ ከእንግሊዝ ሀገር የመጣችሁን መኪና ሊመለከቱ ወጡ መኪናዋን ይዟት የመጣው /Bentley/ ቤንትሌይም የሚገባውን ገለፃ ሰጠ ምኒልክም እየተዟዟሩ ዝቅ ከፍ እያሉ መኪናዋን በሚገባ ተመልክተው ፍጥነቷንም ለማወቅ «አየህ /Bentley/ ቤንትሌይ እኛ በበቅሎ ከዚህ ገበያ ደርሶ መልስ ግማሽ ሰዓት ይበቃናል የመኪናዋን ፍጥነት ማወቅ እንድችል ገበያው ዳር የሚሸጥ አትክልት አለና ሄደህ በመኪናህ እሱን ይዘህ ና?» አሉት: ፈረንጅ ተንኮለኛ ነውና እንዳያሞኙኝም ብለው አብረው ሁለት መኳንንቶቻቸውን ላኩ ቤንትሌይም ከነመኳንንቱ የተላከው ቦታ በፍጥነት ደርሶ መጣ ምኒልክም ሰዓታቸውን አይተው «ጥሩ ነው 6 ደቂቃ ሆናችሁ» አሉ: ከዚያም ምኒልክ መኪናዋ ላይ ወጥተው ከነጂው ጐን ተቀመጡ መኪናዋም ከቀስታ ፍጥነት ተጀምሮ እስከ መጨረሻ ፍጥነት ድረስ እየተነዳች የአዲስ ዓለምን መንገድ አስር ማይል ሄደው ተመለሱ: ከዚህም ቀን በኋላ አጼ ምኒልክ መኪናዋን መንዳት ተለማምደው ለፈተና ቀርበው ሁለት ሰዓት ሙሉ በሚገባ በመንዳት ችሎታቸውን አሳዩ:: ሄልም በመጽሐፉ ''ፐርፌክት ድራይቨር'' /Perfect Driver/ ብሏቸዋል ::በምስሉ ላይ የምንመለከታት መኪናም በምኒልክ ዘመን ከገቡ አምስት መኪናዎች መካከል አንዷ ስትሆን በአሁኑ ሰዓት በብሔራዊ ሙዚየም ግቢ ውስጥ ትገኛለች:: ይች መኪና ዘንድሮ 108 ዓም ሞላት! መኪናዋ ወደ ሃገር ስትገባም በግራና በቀኝ የኢትዮዽያ እና የእንግሊዝን ባንዲራ አንጠልጥለውባት ነበር::

ትልቅ ራዕይ የነበራቸው የቀደሙት አባቶቻችንን እናከበራለን እናፈቅራለን::












No comments:

Post a Comment